Saturday, June 2, 2012

ስነ-ግጥም…የውበት ልቀት ነው

   ቦንቡን 
ቦንቡን  ካልፈራኸው  ንቀል  ከእንብርቷ
ይቆም  ከመሰለህ  ውበት  መለከቷ
በሸንቃጣ  ወገብ  እንዲህ  ተሞናድላ
በእንጆሪ  ከንፈር  በረዶውን  ስላ
ደረቷ  ሚሳኤል  መያዙን  ሳታውቀው
በአይኗ  ወላፈን  ፍቅርህን  ሳትፈጀው
መሞትን  ከመረጥክ
ትግደልህ  ብያለሁ  እሷም  እንድትገልህ  አንተም  እንደመረጥክ ……


 አቤት ስልጣኔ
የጆሮ ተወዶ  ዘንድሮ  ጉድ ፈላ
ምንስ  የቀረ  አለ  ያልተባሳ  ገላ
ውበት ነው፣እብደት  ነው  ወይስ  ስልጣኔ
ይህው  ጉድ  አሳየኝ ዝቅ  ብሎ  አይኔ
እምብርት  ወግ  ደርሶት  ጉትቻ  አጠለቀ
ተገንጦ  በይፋ  ይህው  ፀሀይ  ሞቀ
ቦዲ  የተባለው  መላ  ቅጡ  የጠፋ
ጡቶቿን  አጋልጦ  ያሳያል  በይፋ
ሚኒ  ደሞ ተብሎ  ጣል  የተደረገው
ሀፍረተ  ስጋዋ ይህው  አጋለጠው።

                                                                             የበረሃዋ ገነት
ከወደ ምስራቅ ጸሀይ መውጫ
ያ'ድማስ ጮራ ህብር መገለጫ
ያላፊ አግዳሚው ፍኖት መሳለጫ
የከረዩ ውበት ያ..ክምክም ጎፈሬ
የኢቱ የአፋር ካፎት የሻጠው ጊሌ
የብሄር ስብጥር የግራር ዛፍ ፍሬ
ከበረሃ መሀል ያለሽው መንደሬ
የ'ትብቴ ማረፍያ እልፍ ዓለም ክትሬ
ከፈንታሌ ጋራ ካዋሽ ወድያ ማዶ
ህብረት እንደ ማገር በፍቅርሽ ተገምዶ
የእህል ውሀ ነገር ካድማስ ወድያ ማዶ
ልቤን ካንቺው ትቼ አካሌ ተሰዶ
ፈገግታ§ን ውÂ ደስታው ከኔ ርቆ
ድንገት ከሳሎኔ ከመስታወት ቆሜ
ጥርሴ ላይ የቀረ ያኖርሺው ማተቤ
ተገልጦ የማያልቅ የህይወት አልበሜ
የማንነት ድርሳን መለያ ቀለሜ
ተዳፍኖ ያለውን የልጅነት ህልሜን
ከፍቼው ልተርክ የትዝታን ኪዳን
ጨልፌው ለመጋት ጥሜን ለአመሌ
ብእር ጦሬን ሰበኩ ዝምታን ሰብሬ፡፡
                                           ከስንኝ ቋጥሬ ቃላት ብዘራልሽ
አደባባይ መሐል ማ‘ሌት ብቆምልሽ
አልሆንልህ አለኝ ጣፋጭ እንደምርትሽ፡፡
መርቲ መተሐራ
አንቺ ገነት የበረሀ
የመቻቻል ባህል የመኖር ስንክሳር
  የሰርቶ ማደግን ካሰቡት የማደር
የእንግዳ አቀባበል መልካም ስነምግባር
እንደ ፈንታሌ ጋራ ዙርያሽ ገዝፎ
ያለ ከልካይ ባዋጅ አየር ላይ ተንሳፎ
 አዋሽ ሆደ ቡቡ አዋሽ ዝምተኛ
አዋሽ ሁላ ሁሉ አዋሽ ሚስጥረኛ
አዋሽ አይታክቴ ምድርሽን ሰንጥቆ
የተጠማን ገላ አንጀት ሆድ አርሶ
አፈርሽን ረስርሶ
በእድገት ላይ ጸጋ ውበትሽን ጨምሮ
ወዛደርሽ ወዙን ሳይቆጥብ ገብሮ
ነገውን በተስፋ በሙዳዩ ቋጥሮ
ፍቅር ሲያስተሳስር ሰግሮ
ዘመን ዘመን ተካ ባ'ንድነት ጠንክሮ፡፡
መርቲ መተሐራ
አንቺ ገነት የበረሀ
የአድባር ከራማሽ ቆሌ
ከጂንፉ ጋራ እስከ ፈንታሌ
ከአባድር እስከ ጮሬ
የለምለም ቄጤማው የአዕዋፋት ዝማሬ
ከበሰቃው ማዶ
ውበትሽ አፍ ገዝቶ
ሲናገር ሰማሁት
ፍቅር ጉልበት ሆኖት፡፡
መርቲ መተሐራ
አንቺ ገነት የበረሀ
ከሙቀትሽ ሞቀን
በንፍጦ ግንፍሌ
ከወንዝሽ ቦጭርቀን
ከመስክሽ ፈንጥዘን
ከስኳርሽ ልሰን
ሸንኮራሽን ግጠን
ስንፈልግ ተጣልተን
ያለ ሽማግሌ ከዋርካው ስር ታርቀን
አሳድገሽናል በመቻቻል ሪቫን
በፍቅርሽ  ተቋጥረን፡፡
አላሳፈሩሽም ወንዝሽን ተሻግረው
አንድ ነው ህልማቸው
አንድ ነው ቋንቋቸው
    መሃላ ቃላቸው
ፍቅርን ይሰብካሉ
ተካፍሎ መብላትን
   ላ‘ለም ያሳያሉ፡፡
እንዲህ እንዳሁኑ ዝናሽ በኛው ገኖ
    ፍቅርሽ እንደ በሰቃ ሰፍቶ
        ኑሪልን በእጥፍ ተባዝቶ፡፡  
 
 

                                                 ጥላ….ሁን ለነፍሴ


ዘመን ዘመነና ከግዜ ደጃፍ ላይ
ትዝታን ቀስቅሶ አይኔ እውነቱን ሊያይ
ለእድሜ እድሜ ይስጠው ለዚህ ቀን ካበቃኝ
እፎ…ይ ልበል በቃ ቋጥሬልህ ስንኝ፡፡
ነፍሴ ጮቤ ረገጠች
ሲቃ ተናነቃት ልቤም ተባረከች
ላለፉት ጣፋጭ ግዜያቶች
ለመድረክ ላይ ገድልህ
አንተን ልታስብህ ቃልት አጣችለት
ደፍሬ ልድፈርህ ነፍሴ ደስ ይበላት፡፡
‘ዋይ…ዋይ ሲሉ የርሀብን ጉንፋን ሲስሉ’
አብረህ ብታለቅስ ቢመጣብህ ምስሉ
‘እሩቅ ምስራቅ’ ሄደህ በመንፈስ አፍቅረህ
በየጦር ግንባሩ በወኔ ታጅበህ
‘ገንዘብ አውጡ ስሩ’
‘ቀጠሮም አክብሩ’
ብለህ አስተምረህ
ካዘነው ስታዝን ከሳቀውም ስቀህ
በዜማ ጽላጼ ለኛነት ታድመህ
እልፍ ሳትነጥፍ አግተህ
ጥ…ላሁን አለችህ እናትህ
ሀሴት ስንሞላ ታይቷት ጥላነትህ፡፡
የልጅነት ግዜን ያፍላነት ቡረቃን
የጣፋጭ ትዝታን የማይጠገብን
በተቀደሰው በሞቀው ፍቅራችን
እጃችን ተቋልፎ አንገት ላንገት ታንቀን
እንባ ግድቡን ጥሶ
ጉንጫችን ረስርሶ
“የህይወቴን ህይወት” እኩል ዘመርንበት
ትፍስትን ለግሶ ሊያገባን ከገነት፡፡
አወይ የመሰጠት መታደል ብዛቱ
እንደ ፏፏቴ ሲፈስ ቃላት ካንደበቱ
በርቦ ተቆንጥሮ ላያልቅ ደግነቱ
ግማሽ ዘመን ሙሉ
እመድረክ ላይ ነግሰህ
ደንሰህ አልቅሰህ
እኛን መስለህ እኛን ኖረህ
ውስጣችን አንኳኩተህ
እርግጥ ነው……
ሰው መቼም ሞትን ይሞታል
ያለነው በፊትም
ሞትን ግን ማሸነፍ
በስራ ተግባሩ
አንተ ድል አድርገህ
                 ዘመን ሲሻገሩ
አየሁት በግርምት እስከሙሉ ክብሩ
እድሜ ጠግቦ ዛሬ በዳግም ትንሳኤ
                ሞትና ልደቱ፡፡
አሀዱ እንዳልክባት እንደ“ጥላ ከለላ”
           ሺ ዘመን ትኖራለህ
ቅርጽ ነህ ላገርህ ሙሽራ ሁን ለኛ፡፡
*   *   *
አደም ሁሴን

እሳት ወይ አበባ


እሳት ወይ አበባ

 ሌት ከዋክብቱ  እንደ ፀደይ
አጥለቅልቆን  በቀይ አደይ
ሰማዩ  ሥጋጃ  አጥልቆ
ተሽለምልሞ  አንጸባርቆ
ፈክቶ አሸብርቆ  ደምቆ
በአዝመራ  በአጥቢያ  ዐፀድ  ሰፍኖ
የዓደይ  አዝርዕት  ተከሽኖ
በዕንቁጣጣሽ  ሰብል  ታጥኖ
ኢዮሃ  አበባዬ  ሆኖ፥
ጨረቃዋ  ከቆባዋ፥  ከሽልምልሚት  እምቡጧ
ብላ ከሰንኮፈንዋ፥ ተንዠርግጎ የእንኮይ ቡጧ፥
ድንግል  ጽጌ-ረዳ  ፈልቃ
ፍልቅልቂት  ድምቡል ቦቃ
ተንሠራፍታ  የአበባ  ጮርቃ፥
ታድያን  ብሌኑ  የጠጠረ
ባሕረ-ሃሳቡ የከረረ
የውበት ዓይኑ የታወረ
ልበ-ሕሊናው  የሰለለ
አይ፥ አበባ አይደለም አለ፤
አይ፥ እሳት አይደለም አለ፤
ያልታደለ።
ሰማይ  ጨለማ  ነው እንጂ፥  እሳት አደል ብሎ ካደ
እቶን  ባይኑ  እየነደደ።
ከዋክብቱ  እንደ  ችቦ
በነበልባል  ወርቀ  ዘቦ
ከፅንፍ  ፅንፍ  አውለብልቦ
ደመራው  እየተመመ
እየፋመ  እየጋመ
ደመና  እንደንዳድ  ሲነድ
መንጸባርቅ  ሰደድ  ሲወርድ፥
በራሪ  ኮከብ  ተኩሶ
በአድማሳት  እሳት  ለኩሶ
ይኸ እንደኔና  እንዳንቺው፥  የውበት ዓይኑ  የሰለለ
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ፥  እሳት እኮ አይደለም አለ፥
ያልታደለ።

ይቅር ብቻ  አንናገርም፥
እኔና  አንቺ  አንወያይም፤
ለውይይት  አልታደልንም
እንዲያው ዝም፥ እንዲያው ዝምዝም።
አበባ አንሆን ወይ እሳት
ተጠምደን  በምኞት  ቅጣት
ሰመመን  ባጫረው  መዓት
ዕድሜ አችንን እንዳማጥናት፤

እሳት አንሆን ወይ አበባ
በሕቅ  እንቅ  ስንባባ
ባከነች  ልጅነታችን፥ እየቃተትን ስናነባ
ሳንፈጠር  በሞትንባት
ሳናብብ  በረገፍንባት
ሳንጠና ባረጀንባት
አበባ ወይንም እሳት፥  መሆኑን ብቻ አጣንባት።
© © ©

ከጸጋዬ ገብረ መድኅን


 

No comments:

Post a Comment